መግለጫውን የሰጡት ከዚህ ቀደም የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበሩና አሁን ላይ ተቀማጭነታቸውን እንግሊዝ ባደረጉት የቴአትር ጥበብ ምሁር በሆኑት አቶ አስተዋይ መለሰ፣የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት በሆኑት በዶክተር ሀብቴ ዱላ እና የአካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክተር በሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ካሳሁን አቤ አማካይነት ሲሆን በመግለጫው ላይ የዋልታ ቴሌቪዢን ፣የባላገሩ ቴሌቪዢንና የአርትስ ቴሌቪዢን ጋዜጠኞች ታድመውበታል፡፡ መግለጫው በሚከተለው መልኩ ቀርቧል፡፡
የሙርሲ ብሄረሰብ በደቡብ ኢትዮጵያ ክፍል በደቡብ ኦሞ ዞን ውስጥ ከሚገኙት አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች መከካል አንዱ ነው፡፡ ይህ ብሄረሰብ በኢትዮጵያ ደረጃ የውጭ ቱሪስቶች ከሚጎበኟቸው መካከል አንዱ ሲሆን የራሱ የሆነ የአኗኗር ባህልና ዘይቤ ያለው ብሄረሰብ ነው፡፡
ብሄረሰቡ ያለውን ሀገር በቀል ዕውቀት እና ዕምቅ ሀብት በተሻለ መንገድ በመሰነድ ለትውልድ ለማሸጋገር የሚያግዝ አበረታች ፕሮጀክት በብሄረሰቡ ተወላጅ በሆነው በኦሊሶራሊ ኦሊቡዪ ሊጸነስ ችሏል፡፡ የፕሮጀክቱም
መጠሪያ “ተንቀሳቃሽ ትምህርት ለመላው ሙርሲ” የሚል ነበር፡፡ ኦሊ አካባቢውን በትምህርት ለመለወጥ የተንቀሳቀሳሽ ትምህርት ቤት ጽንሰ ሀሳብን ይዞ አጋዥ በመፈለግ ላይ እያለ በጉብኝት አጋጣሚ ባወቃቸው የውጭ ሀገር ዜጎች የተወሰነ ዕርዳታ በመታገዝ ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ክፍል ለማስተማር የሚያስችል የመማሪያ መጽሀፍ በሙርሲ ቋንቋ ለማዘጋጀት ችሏል፡፡
በሌላ አጋጣሚ ካገኛቸው ኢትዮጵያውያን እና የውጭ ሀገር ዜጎች ጋር በመሆን የሙርሲን ባህል ሊያስተዋውቅ ሊያሳድግ፣ ሊሰንድ፣ለቀሪው ዓለም እና ለመጪው ትውልድ ሊያስተላልፍ ብሎም የተንቀሳቃሽ ትምህርት ቤት ስርዓት የመዘርጋት ህልሙን ወደ ፍሬያማነት ሊለውጥ የሚችል የቴአትርና ዘጋቢ ፊልም ፕሮጀክት በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ ይህም ጥረቱ ለፍሬ እንዲበቃ የአውስትራሊያ፣አሜሪካና እንግሊዝ ጎብኚዎች ድጋፍ በእጅጉ የሚደነቅ ነበር፡፡
ኦሊ ከሙርሲ ብሄረሰብ መካከል ባህር ተሻግሮ ዕውቀት ቀስሞ የተመለሰ የመጀመሪያው የብሄረሰቡ ተወላጅ ነው፡፡ በተጨማሪም ከአውስትራሊያ ሚሲዮናውያን ጋር በመሆን ለሁለት ዓመታት ወደ አውስትራሊያ አቅንቶ የእንግሊዘኛ ቋንቋን ተምሮ ተመልሏል፡፡ ኦሊ ያለውን አቅም በሙሉ በማስተባበር ማህበራዊ ሃላፊነቱን ፣ የአባትነት ግዴታውን ለመወጣት በኢትዮጵያ በተለይም በደቡብ ክልል ከሚገኙ መካነ አዕምሮዎች ጋር በጥምረት እየሰራ ይገኛል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኦሊ ከሌሎች አሜሪካውያን ጋር በመተባበር ስዕላዊ የመማሪያ መጽሀፍትን በሙርሲ፣በአማርኛ እና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች ጽፎ አሳትሟል፡፡ ለቴክኖሎጂ ልዩ ፍቅር ያለው ኦሊ በካሜራ ጥበብ በመማረክ ከጎብኚዎች በዳረጎት በሚያገኛቸው ያረጁ ካሜራዎች በመታገዝ ስለፊልም አቀራረጽ በቂ ሊባል በሚችል ደረጃ ራሱን ካስተማረ በኋላ መቀመጫውን ለንደን ፣ዩናይትድ ኪንግደም ካደረገው የ”ያንግ ኤንድ ያንግ ፊልም ፕሮዳክሽን “ ባለቤት ከሆኑት ቤን ያንግ ጋር የተፈጠረለትን የትውውቅ አጋጣሚ በመጠቀም በስምንት ዓለም አቀፍ የፊልም ፌስቲቫሎች ላይ ዕጩ የሆነ፣በአራቱ ላይ ደግሞ በአሸናፊነት የተመረጠ “ሹቲንግ ዊዝ ሙርሲ “የተባለ ዘጋቢ ፊልም ሰርቶ እጅግ አድናቆትን አግኝቷል፡፡ ከዚህ ፊልም ስኬት በኋላ ኦሊ በአውሮፓ ፣በአሜሪካ፣በካናዳ፣በአፍሪካ እንዲሁም አውስትራሊያ በማቅናት ህልሙን፣ ፊልሙንና ህዝቡን አስተዋውቋል፡፡
የኦሊን ህልም ዕውን ለማድረግ የሚተጋው ቤንም በአካባቢው ያሉ በምርምር፣ በፊልም፣በቴአትርና በሚዲያ ዘርፎች የተሰማሩ ባለሙያዎችን በማሰባሰብ በኦሊ መሪነት የሙርሲን እውነተኛ ገጽታ ሊያሳይ የሚችል የምርምር ፣የቴአትር አቅርቦትና የዘጋቢ ፊልም ፕሮጀክት ነደፈ፡፡ ንድፉም በUniversity of London School of Oriental and African Studies ተቀባይነትን አገኘ፡፡ የኢትዮጵያውያንና የምዕራብያውያንን ምሁራን ያካተተው ይህ አዲስ ስብስብ የኦሊን ህልም ተጋርቶ ግቡን ለማድረስ የበኩሉን ድጋፍ አድርጓል፡፡
ለኦሊ አጠቃላይ ህልም ስኬት ያግዝ ዘንድ በቅድሚያ በመዲናችን አዲስ አበባ የሚገኙ የቴአትር ቤቶችን ማስጎብኘትና የተወሰኑ ትውፊታዊ ቴአትሮችን እንዲመለከት በማድረግ ከጥበቡ ጋር እንዲተዋወቅ ተደረገ፡፡ በመቀጠልም በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የቴአትር ጥበብን የሚያስተምሩ ምሁራን አባል የሆኑበት የአዲሱ የባህል ፕሮጀክት ሁነኛ የቴአትር ማሰልጠኛ ፍለጋ መስፈርቶችን አውጥቶ መፈተሸ ሲጀምር ቀዳሚ ምርጫው ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ሊሆን ቻለ፡፡
ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲን ሲቀላቀል በውስጡ ታምቆ ያለውን ቱባ የሙርሲ ባህል እንዴት በቴአትር መልክ ሊጽፍ እንደሚችል እና እንዲሁም ስለትወና ምንነት እጅግ መሰረታዊ የሆኑ ክህሎቶችን ተምሮ ዓለምን የዞረበትን ዘጋቢ ፊልም በኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ውስጥ አሳይቶ ትልቅ የስኬት መንፈስ ተላብሶ ወደ ሙርሲ ምድር ተመለሰ፡፡
ኦሊ ወደ ሙርሲ በመመለስ ከጸኀፊ ተውኔት፣አዘጋጅ እና የቴአትር ጥበብ መምህር ከሆነው አቶ ተስፋሁን ጋር በመሆን “ቲራኒያ ኮ ኮይሳኒ “ ወደ አማርኛ ሲመለስ “ዳኛው” በሚል ርእስ በሙርሲ ብሄረሰብ የማንነት መሰረቶች ላይ የሚያጠነጥን የመልቲ ሚዲያ ቴአትር ቅርጽን የያዘ ተውኔት መጻፍ ጀመረ፡፡ ከዚህ በኋላ አቶ ተስፋሁን በግል ጉዳይ ከሀገር በመውጣቱ ምክንያት የስልጠናና የጽሁፍ ስራው በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ዮሴፍ በሀይሉ እና ሜሮን ተስፋዬ እንዲሁም በቀድሞው የዩኒቨርሲቲው መምህርና አሁን ላይ ተቀማጭነቱን እንግሊዝ ባደረገው የቴአትር ጥበብ ምሁር አስተዋይ መለሰ አጋዥነት ውጥኑ ከዳር ደረሰ፡፡
የቴአትር አቅርቦቱ የሙርሲን ታሪክ ስለትወና የላቀ እውቀት በሌላቸው የሙርሲ ብሄረሰብ ተወላጆች በማስተወን በሀገረ እንግሊዝ የሚገኘውን የመልቲ ሚዲያ ቴክኖሎጂን በመጠቀም በኢትዮጵያ የቴአትር ታሪክ ውስጥ እምብዛም ያልተለመደ ቅርጽና ይዘት ያለው አዲስ አቀራረብ ለማሳየት አልሟል፡፡ ይህ ሀምሌ 24/2014 ዓም ለእይታ ለመብቃት እየተሰናዳ ያለው ቴአትር ኢትዮጵያዊ የቴአትር ቅርጽን ለመፈለግ የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዝ ይታመናል፡፡ በመቀጠልም ከሙርሲ ሰባት ወጣቶችን የመምረጥ እና ወደ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ይዞ የመምጣት ስራውም በስኬት ተጠናቀቀ፡፡ እነዚሁ ወጣቶች ላለፉት አራት ወራት መቀመጫቸውን ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በማድረግ ብርቱ ስልጠና እንዲወስዱ ተደርጓል፡፡
ይህ ቴአትር ሀምሌ 06/2014ዓም ለብሄረሰቡ ተወላጆች የሚቀርብ ሲሆን የብሄረሰቡ አባላትን ይሁንታና ግምገማ ካገኘ በኋላ ለቀሪው ኢትዮጵያዊ እና ለመላው ዓለም የሚቀርብ ይሆናል፡፡ ከሙርሲ መንደር በመቀጠል ሀምሌ 17/2014 ዓም ለወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ ይቀርባል፡፡ በመጨረሻም ሀምሌ 24/2014 ዓም በብሄራዊ ቴአትር ይቀርባል፡፡ በዕለቱም በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ አንጋፋና ጀማሪ ከያንያን ፣ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የፖለቲካ ተንታኞች፣የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተወካዮችና ሌሎች ኢትዮጵያውያን ጭምር በነጻ ይታደሙበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በቀጣይም በአውሮፓ ከተሞች፣አሜሪካ፣ ካናዳ እና አወስታራሊያ ይቀርባል፡፡ በዚህም ሀገራችን በማስተዋወቅ ረገድ ጉልህ ሚና ይኖረዋል፡፡