አዲስ ማለዳ በዛሬው ዕትሙ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲን አስመለክቶ ያወጣውን ዘገባ መነሻ በማድረግ የሚዲያውን ከፍተኛ የማኔጅመንት አካል የሆኑትን አቶ ሚካኤልን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ፋሪስ ደሊል በስልክ አነጋግረው የጋዜጣውን አዘጋጅ አድራሻ የተቀበሉ ሲሆን ዋና አዘጋጁን አቶ ቢኒያም በተደጋጋሚ ለተደረገላቸው የስልክ ጥሪ ሙከራ ምላሽ ሊሰጡ ያልቻሉ ሲሆን በአንጻሩ በSMS በላኩት የጽሁፍ መልዕክት “ አሁን ማነጋገር ስለማልችል ስጨርስ እደውላለሁ “ የሚል ምላሽ ከመስጠት ውጭ እስካሁን ድረስ ተጨማሪ ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡
በሌላ በኩል የጽሁፉ አቅራቢ የሆነው አቶ ኢዮብ ትኩዬ ለመጀመሪያ የስልክ ጥሪ ምላሽ የሰጠ ሲሆን በሰጠውም ምላሽ ግለሰቡ የዩኒቨርሲቲው ናቸው ያላቸው ሁለት የስልክ ቁጥሮች ላይ ለመደወል እንደሞከረ ቢገልጽም ቁጥሮቹን ለመናገር ፈቃደኛ አይደለም፡፡ ለተጨማሪ ማብራሪ ድጋሚ ቢደወልለትም ስልክ ለማንሳትም ሆነ በSMS ምላሽ አልሰጠም፡፡
በመሆነም ይህንን ተከትሎ ዩኒቨርሲቲው የሚከተሉትን እርምጃዎች ወስዷል፡-
1ኛ . የዩኒቨርሲቲው ዋና ሬጅስትራርና የኮሌጅ ሬጅስትራር ቢሮዎች ተገቢው የማጣራት ስራ እስኪሰራ ድረስ ሙሉ በሙሉ በሙሉ እንዲታሸጉና ተገቢው ጥብቅ የሆነ ጥበቃ እንዲደረግላቸው ተደርጓል፡፡
2ኛ .የተማሪዎች የመረጃ ቋት የሆነው SIMS (Students’ Information Management System ) ተገቢው ማጣራት እስኪደረግ ድረስ እንዲዘጋ ተደርጓል፡፡
ስለሆነም ባልተረጋገጠ መረጃ ማህበረሰቡን ማደናገር እንዲሁም ሚዛናዊ ያልሆነ መረጃ ካልታወቀ ምንጭ ይዞ ማቅረብ የተቋሙን ስምና ዝና ከማጉደፉም በተጨማሪ ከዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ጀምሮ እስከ ሬጅስትራር ሀላፊ ድረስ መረጃውን ለማጣራት ምንም ዓይነት ጥረት ሳይደረግ የሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ የትውልድ ማፍሪያ የሆነውን አንድ ተቋም በዘፈቀደ ስም ማጥፋት ተገቢነት እንደሌለው ለመላው ህዝባችን ለማሳወቅ እንወዳለን፡፡
ስለሆነም በቀጣይ በምናደርገው ዝርዝር የማጣራት ስራ የቀረበው መረጃ እውነት ሆኖ ካገኘነው በድርጊቱ ተዋናዮች ላይ ተገቢውን አስተዳደራዊና ህጋዊ ርምጃ የምንወስድ ሲሆን በአንጻሩ ግን የሀሰት ውንጀላ ሆኖ ካገኘነው ዩኒቨርሲቲው አግባብነት ያለውን ህግ ተከትሎ ጉዳዩን ለህግ የሚያቀርብ መሆኑን እንገልጻለን፡፡
በዚህ አጋጣሚ እስካሁን ባለው ሂደት ዩኒቨርሲቲው ለተመራቂ ተማሪዎች ጊዜያዊ የትምህርት ማስረጃ (Temporary Degree ) ብቻ እየሰጠ መሆኑን እና ኦሪጅናል ዲግሪ በተመለከተ ከብርሀንና ሰላም ማተሚያ ቤት ጋር ውል ፈጽሞ በማሳተም ሂደት ላይ መሆኑን እየገለጽን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ኦሪጂናል ዲግሪ ማስረጃ አለኝ ብሎ የሚያቀርብ ግለሰብ ካለ የትምህርት ማስጃው ሕገወጥ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡