ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ጋር በመተባበር የቅድመ- መደበኛ ትምህርት የጉራጊና መጽሃፍት ትውውቅ የአሰልጣኞች ስልጠና ሰጥቷል፡፡
በዚህም የስልጠና መድረክ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው የምርምር እና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ዮሃንስ ገብሩ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ዘርፉ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ መሆኑን አስታውሰው ከእነዚህም መካከል በ19 ትምህርት ቤቶች የዩኒቨርሲቲውን መምህራን በመላክ የማጠናከሪያ ትምህርት (ቱቶሪያል) መስጠቱን፣ ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች የማበረታቻ ሽልማት ማበርከቱን እንዲሁም አሁን ላይ በጉብሬ ከተማ ላይ በማስገንባት ላይ ያለው የማህበረሰብ ትምህርት ቤት ዩኒቨርሲቲው እያደረገ ላለው ድጋፍ ዋነኛ ማሳያ ነው በማለት ገልጸዋል፡፡
ዶክተር ዮሀንስ አያይዘውም በጉራጊና ትምህርት ዝግጅት እንቅስቃሴም ዩኒቨርሲቲው ከፊደል ቀረጻ ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን ማድረጉን አብራርተዋል፡፡ ም/ፕሬዝዳንቱ አያይዘውም በጉራጊና ቋንቋ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ስልጠና ላይ የተሳተፉት ሰልጣኝ መምህራኖች ተገቢውን እውቀት በመቅሰም የመማር ማስተማር ሂደቱን እንዲያከናውኑ አሳስበዋል፡፡
የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ሃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም በበኩላቸው የጉራጊና ቋንቋ በተለያዩ ምክኒያቶች ወደ ስርዓተ-ትምህርት ትግበራ ሳይገባ መቆየቱን ገልጸው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በተደረጉ ሁለንተናዊ ጥረቶች በ2013 ዓ.ም የጉራጊና የፊደል ገበታ የማስጠናት ስራዎች መጀመሩን ጠቅሰው በ2014 ዓ.ም የትምህርት ዘመን የቅድመ መደበኛ ትምህርት የመጽሃፍት ዝግጅት መደረጉንና በ2015ዓ.ም የትምህርት ዘመን በ20 ትምህርት ቤቶች የሙከራ ትምህርት ሲሰጥ መቆየቱን አብራርተዋል፡፡
አቶ መብራቴ አያይዘውም ከዛሬው የጉራጊና ቋንቋ የቅድመ መደበኛ ትምህርት የመጽሃፍ ይዘት ትውውቅ በኋላ በሁሉም የዞኑ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ህዳር 03/2016ዓ.ም ፕሮግራሙ በይፋ ይጀመራል ብለዋል፡፡ በ2016ዓ.ም የትምህርት ዘመንም የአንደኛ ክፍል የጉራጊና ቋንቋ የሙከራ ትምህርት እንደሚሰጥ አሳውቀዋል፡፡
በዞኑ ትምህርት መምሪያ የስርዓተ ትምህርት ክፍል ሃላፊ የሆኑት ወ/ሮ ገነት ደምስስ በበኩላቸው ህጻናት ትምህርት በሚጀምሩበት በለጋ ዕድሜያቸው በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው መማራቸው ትርጉም ከመፈለግ ይልቅ ቀጥታ ትምህርቱን እንዲገነዘቡት እና እንዲረዱት በማድረጉ የትምህርት ፍላጎታቸው እንዲጨምር እና የወደፊት የትምህርት ርዕይ እንዲሰንቁ ያደርጋቸዋል ብለዋል፡፡ ወ/ሮ ገነት አክለውም ህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ሲማሩ ለትምህርት ጥራት ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡
በስልጠናውም ላይ ከዞኑ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ መምህራን ፣የትምህርት ቤት ሃላፊዎች እና የተለያዩ የባለድርሻ አካላት ተሳትፈውበታል፡፡
ለጥበብ እንተጋለን!
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት