ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በዛሬው ዕለት በቅድመ ምረቃና በድህረ ምረቃ ፕሮግራሞች በመደበኛውና በተከታታይ የትምህርት ዘርፍ ያሰለጠናቸውን በድምሩ 1195 ተማሪዎችን እጅግ ደማቅ በሆነ ሁኔታ አስመርቋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በቅድመ ምረቃ ፕሮግራም በ43 የትምህርት ክፍሎች ወንድ 824 ሴት 288 በድምሩ 1112 እንዲሁም በድህረ ምረቃ ፕሮግራም በአስራ ሁለት የትምህርት ፕሮግራሞች ወንድ 66 ሴት 17 በድምሩ 83 በአጠቃላይ በሁሉም ፕሮግራሞች ወንድ 890 ሴት 305 በድምሩ 1195 ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡
በአጠቃላይ ድምር ውጤት በ31 የትምህርት ዓይነቶች A+ በማምጣትና በድምር ውጤት 3.98 በማምጣት ተማሪ ተመስገን ዮሴፍ ድጋፌ ከቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ከአካውንቲንግና ፋይናንስ የትምህርት ክፍል የዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት ክቡር ዶክተር ደረጀ ዱጉማ የኢፌዴሪ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታ እና የወልቂጤ ዪኒቨርሲቲ የስራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ባስተላለፉት መልዕክት የእለቱ ተመራቂዎችና የተመራቂ ተማሪ ቤተሰቦችን እንዲሁም መምህራንን እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል፡፡
ክቡር ዶክተር ደረጀ ዱጉማ አያይዘውም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ወደ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ ከፍተኛ ጥረት ለሚያደርጉ ሀገራት በኢኮኖሚው፤ በማህበራዊና በፖለቲካዊ ዘርፍ እያስመዘገቡት ያለውን ዕድገት ለማፋጠን ትምህርት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ገልጸው በተለይም በዕውቀት ያደገ፣ በክህሎት የዳበረ፣ በአስተሳሰቡ የበለጸገ፣ በመልካም ስነምግባር የታነጸ እንዲሁም ቴክኖሎጂን የመፍጠርና የመጠቀም አቅሙ ከፍ ያለ ትውልድ በማፍራት ረገድ ትምህርት የሚኖረው አበርክቶ በእጅጉ የላቀ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በዚህም መሰረት የኢፌዴሪ መንግስት ለዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠት ገበያው የሚፈልገውን ምሩቃንን በብዛትና በጥራት በማምረት ረገድ ሰፊ የሆነ ትኩረት በመስጠት በመስራት ላይ እንደሚገኝ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ ገልጸው በ2014ዓ.ም. የትምህርት ዘመን እንደ ሀገር የደረሰብንን የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች የውጤት ስብራት ለመጠገን የኢፌዴሪ መንግስት ችግሩን በውል በመረዳት ከቅድመ መደበኛ ጀምሮ ትምህርት በስፋት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች ላይ ሰፊ የሆነ ትኩረት በመስጠት፣ በተለይም አብዛኛዎቹ ትምህርት ቤቶች ደረጃቸውን ያልጠበቁ በመሆናቸው የትምህርት ቤቶችን የደረጃ ማሻሻል ስራዎችን በስፋት በመስራት ረገድ በትምህርት ሚኒስቴር ደረጃ ማህበረሰቡን ባሳተፈ ሁኔታ ከፍተኛ የሆነ የህብረተሰብ ንቅናቄ ስራዎች በመሰራት ላይ መሆናቸውን ዶክተር ደረጀ ገልጸዋል ፡፡
ዶክተር ፋሪስ ደሊል የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት በበኩላቸው ባስተላፉት መልዕክት የዛሬ ተመራቂዎች ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ እናንተም በመላው ሀገራችን ካሉት ተመሳሳይ ፕሮግራም ከሚከታተሉት ሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ጋር አንድ አይነት ፈተና በተመሳሳይ ጊዜ ፍጹም ሊባል በሚችል ጥብቅ ዲሲፕሊን ተፈትናችሁና ተስፋ ሰጪ ውጤት አምጥታችሁ ያለፋችሁ የጥንካሬ ተምሳሌት ናችሁና እንኳን ደስ ያላችሁ ካሉ በኋላ ይህ ውጤት እንዲመጣ የተማሪዎቻችን ጥረት አይተኬ ሲሆን የመምህራን ድጋፍና ክትትል ፣ የትምህርት አመራሩ ቁርጠኝነትና በሳል አመራር ሰጪነት፣ የተቀረው የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ ክፍል ድጋፍና ክትትልና የቅርብ አጋርነት፣ የስራ አመራር ቦርዱ ስትራቴጂያዊ አመራር ሰጪነት የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከቱን ዶክተር ፋሪስ በመልዕክታቸው ላይ ገልጸዋል፡፡
በምረቃው ስነስርዓት ላይ ክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ ክቡር አቶ ሺሰማ ገብረስላሴ የጉልባማ የቦርድ ሰብሳቢ፣ ክቡር አቶ ኤልያስ ሽኩር የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር፣ የዩኒቨርሲቲው የስራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የዩኒቨርሲቲው የሴኔት አባላት እና ልዩ ልዩ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
ምርቃቱ ከተጠናቀቀ በኋላ የችግኝ ተከላና የዩኒቨርሲቲው ኢንተርፕራይዝ ጉብኝት ተካሂዷል፡፡
ለጥበብ እንተጋለን!
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት