ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ሁለት መቶ ለሚሆኑ ተመራቂ ሴት ተማሪዎች ለሶስት ተከታታይ ቀናት የሚቆይ የፕሬዝዳንሻል ሜንተርሽፕ ስልጠና መስጠት ጀመረ
ስልጠናውን ያስጀመሩት የዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማር ጉዳዬች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ሀብቴ ዱላ ተማሪዎች እስካሁን በግቢው ውስጥ የነበራቸው ቆይታ ስኬታማ በመሆኑ ለመጨረሻዋ የትምህርት መንፈቅ አመት ደርሰዋል በማለት አሁንም ከፊት የሚጠብቃቸውን የመውጫ ፈተና ለማለፍ በተለመደው ብርታታቸው በትጋት እንዲዘጋጁ አሳስበዋል፡፡
የመማር ማስተማር ጉዳዬች ጽህፈት ቤት ሃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ካሳሁን አቤ በስልጠና ማስጀመሪያ መድረኩ የተገኙ ሲሆን ሴትነት በራሱ መሪነት ነው በማለት ዛሬ ጀምሮ የሚሰጠው ስልጠናም ሴት ተማሪዎች ብቁ መሪ በመሆን ከራሳቸው አልፈው ሀገር ለመምራት የሚያስችል አቅም የሚሰጥ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡ ረ/ፕ ካሳሁን አያይዘውም ነገ ብቁና ተመራጭ መሪ ለመሆን የዛሬው የትምህርት ብቃት ዋናው መሰረት ነው በማለት ቀሪውን ጊዜ በአግባቡ ለመውጫ ፈተና ዝግጅት በመጠቀም ሀላፈነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡
የዩኒቨርስቲው የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ኤችአይቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዳይሬክተር ወ/ሮ መሰረት አስራት እንደገለፁት ይህ ስልጠና ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከአለም አቀፍ የትምህርት ተቋም /Institute of International Education/ ከተሰኘ ግብረ-ሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር የተዘጋጀ ነው:: የስልጠናው ተሳታፊ ሴት ተማሪዎች በያዝነው አመት የሚመረቁ ሲሆኑ ስልጠናውም የአመራር ሰጪነት ክህሎታቸውን በማዳበር በየስራ ዘርፉ ሲሰማሩ ብቁ እና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል ያለመ እንደሆነ ዳይሬክተሯ አያይዘው ገልፀዋል፡፡
ስልጠናውን የሚሰጡት የዩኒቨርሲቲው መምህር የሆኑት መምህርት ይገረሙ ክፍሌ እና መምህርት ፌቨን ዬሀንስ ሲሆን "Entrepreneurship, career development and presentation skill" በሚሉ ርዕሶች ላይ የሚያተኩር ነው፡፡