የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የሴቶች ፣ህጻናት፣ወጣቶችና ኤች አይቪ /ኤድስ መከ/መቆ/ዳይሬክቶሬት ከተማሪዎች ህብረት ጋር በጋራ በመሆን ያዘጋጁት ይህ ፕሮግራም የዓለም የኤድስ ቀንን አስመልክቶ “ፍትሀዊና ተደራሽ የኤች አይቪ /ኤድስ አገልግሎት “ ፣ በሴት እህቶቻችን ላይ የሚደርሰውን ጾታዊ ትንኮሳ (የነጭ ሪቫን ቀን) አስመልክቶ“ ሴቶችን አከብራለሁ ጥቃታቸውንም እከላከላለሁ“ በሚል እንዲሁም የአካል ጉዳተኞችን ቀን በማስመልከት “ አካታች የፈጠራ ስራ እና ሽግግራዊ መፍትሄ ለኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተደራሽነት “ በሚል ሶስቱን አንኳር ጉዳዮች በአንድ ላይ በማጣመር በዓሉ በድምቀት ተከብሯል፡፡
በበዓሉ ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው የፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ሃላፊ የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር መለሰ እጥፉ ባስተላለፉት መልዕክት ሶስቱም በዓላት በአንድም ሆነ በሌላ የሚያገናኛቸውና የሚያስተሳስራቸው እውነታ መኖሩን ጠቅሰው ከዚህ ቀደም ኤች አይቪ ኤድስ እንደሀገር በተለይም አምራቹ ዜጋ ላይ እያስከተለ የነበረውን ጉዳት በማጤን ትኩረት ተሰጥቶት ሲሰራ እንደነበረ አስታውሰው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን መዘናጋቶች መስተዋላቸውንና ለበሽታው የተሰጠው ትኩረት አነስተኛ ቢሆንም በአንጻሩግን ኤች አይቪ ኤድስ እንደሀገር እየተስፋፋ መምጣቱን በመግለጽ ትኩረት ልንሰጥበት እንደሚገባና ችላ በማለታችን ምክንያት ብዙ ወገኖቻችንን እያጣን እንደሆነ አጽንኦት በመስጠት ገልጸዋል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰር መለሰ እጥፉ አያይዘውም ለአካል ጉዳተኞች ተገቢውን ድጋፍ ማድረግና ጾታዊ ትንኮሳንም በጋራ ልንከላከለው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የአስተዳደርና ኮርፖሬት ማኔጅመንት ምክትል ፕሬዝዳንት የሆኑት ዶከተር የሻረግ አፈራ በበኩላቸው እንደገለጹት ሶስቱን ፕሮግራሞች በጋራ አጣምረን ማክበራችን ተገቢውን መረጃ ለመለዋወጥ እንደሚያግዝ ገልፀው ተማሪዎች የመጡበትን ዓላማ ሳይዘነጉ ትምህርታቸው ላይ ትኩረት ሰጥተው ለምረቃ እንዲበቁ ራሳቸውን ከኤች አይቪ ኤድስ ጥቃት መከላከል እንደሚገባቸውና ሀገራችንን በልማት ወደፊት ማሻገር ይገባናል በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ የሆኑት ዶክተር አብድረሂም በድሩ በበኩላቸው ኤች አይቪ ኤድስን አስመልክቶ ዳራዊ መረጃውን ሰፋ ባለ ሙያዊና ሳይንሳዊ ትንታኔ የገለጹ ሲሆን ኤች አይቪ ኤድስ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና ስነልቦናዊ ጫናዎችን በዜጎች ላይ እያስከተለ መሆኑን ገልጸው በሽታው ያልጠፋበት ምክንያት በተለይም በወጣቶች አካባቢ በሚታየው ዝንጉነት፣በተወሰኑ ወጣቶች ላይ በሚታየው በሱሰኝነት መጠመድ ፣የአቻ ግፊት ተጽእኖ እና ከባህላችን በማፈንገጣችን ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የሴቶች ፣ህጻናት፣ ወጣቶችና ኤች አይቪ /ኤድስ መከ/መቆ/ዳይሬክተር የሆኑት ወ/ሮ መሰረት አስራት በበኩላቸው እንደገለጹት የዓለም የኤች አይ ቪ/ኤድስ ቀን በዓለማችን ለ35ኛ ጊዜ በሀገራችን ለ34ኛ ጊዜ የሚከበር መሆኑን፣ ዓለም ዓቀፍ የጸረ-ጾታ ጥቃት ቀን በዓለማችን ለ31ኛ ጊዜና እና በሀገራችን ለ17ኛ ጊዜ እየተከበረ መሆኑን እንዲሁም የአካል ጉዳተኞች ቀን በዓለማችን ለ31ኛ ጊዜ በሀገራችን ለ30ኛ ጊዜ እየተከበረ መሆኑን ከግምት በማስገባት ለሶስቱም ጉዳዮች ትኩረት በመስጠት በጥምረት እንዲከበሩ መደረጋቸውን ገልጸዋል ፡፡
ወ/ሮ መሰረት አያይዘውም በዓለም አቀፍ ደረጃ ኤች አይቪ ኤድስ ከአርባ ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ለሕልፈት መዳረጉንና አሁንም ላይ በሀገራችንና በዓለማችን ላይ ከፍተኛ የሆነ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ወ/ሮ መሰረት አያይዘውም በ2014 ዓ.ም 8 ሚሊዮን ሰዎች ላይ በተደረገ የኤች አይ ቪ ኤድስ ምርመራ 35 ሺህ የሚሆኑት ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ መገኘቱን በጥናት መረጋገጡን ገልጸዋል፡፡
ኤች አይቪ ኤድስን አስመልክቶ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ሊያ ታደሰ በቅርቡ እንደገለፁት እ.ኤ.አ በ2021 1.5 ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች አዲስ በኤች አይ ቪ የተያዙ ሰዎች እንዳሉና 650,000 ሰዎች በዚሁ ዓመት ለህልፈት እንደተዳረጉ፤ ኤች አይ ቪ በደማቸው ካለባቸው ሰዎች ውስጥ ደግሞ 28.7 ሚሊዮን የሚሆኑት የፀረ-ኤች አይ ቪ ህክምና እንዳገኙ መረጃዎች ያሳያሉ በማለት ገልጸዋል፡፡
ክብርት ዶ/ር ሊያ ታደሰ አክለውም በሀገራችን የኤችአይቪ የስርጭት መጠን መቀነሰ ቢቻልም አሁንም በየደረጃው ከፍተኛ መዘናጋት እና ቸልተኝነት አለ ብለዋል፡፡ የሀገራችንም የኤች አይ ቪ የስርጭት ምጣኔ 0.93% ሲሆን በዚህ ስሌት 617,921 (62% ሴቶች) በላይ የሚሆኑ ወገኖች ኤች አይ ቪ በደማቸው እንደሚገኝ በ2013/14 የተሰራው ግምታዊ ቀመር ያሳያል ብለዋል፡፡ በ2014 ብቻ በሀገራችን አዲስ ኤች አይ ቪ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 35,000 በላይ መሆኑን ክብርት ዶ/ር ሊያ ታደሰ ገልጸዋል፡፡
በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተከበረው የዓለም ኤች አይቪ ኤድስ ቀን ላይ የመዝጊያ ንግግር ያደረገው የኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት እና እንዲሁም የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ተማሪ ሚካኤል ያቦነሽ ተማሪዎች ራሳቸውን ከኤች አይቪ ኤድስ በሽታ በመጠበቅ ፣ በሴት እህቶቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ጾታዊ ጥቃት በጋራ በመከላከል ለአካል ጉዳተኞች ልዩ ትኩረት በመስጠት በዓሉን እንዲያከብሩ አሳስበዋል፡፡
በመጨረሻም በዓሉን በማስመልከት በኤች አይ ቪ ኤድስ ምክንያት ህይወታቸውን ላጡት ወገኖቻችን የጧፍ ማብራት ስነስርዓት የተከናወነ ሲሆን በዓሉን በማስመልከት ከክብረ በዓሉ አስቀድሞ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ የጋራ የሆነ የጽዳት ዘመቻ አከናውነዋል፡፡ በዓሉን ለማድመቅ በሴት ተማሪዎች አማካይነት እጅግ መሳጭ የሆነ የቴኳንዶ ትርኢትና ልዩ ልዩ ጣዕመ ዜማዎችና ግጥሞች በተማሪዎች አማካይነት ቀርበዋል፡፡