በዩኒቨርሲቲው የሚገኙ የአስተዳደር ሰራተኞች የስራ ሰዓት መቆጣጠሪያ የጣት አሻራ አቴንዳስ በባዮሜትሪክስ ማሽን እንዲሆን በማስፈለጉ በማሽኑ አጠቃቀም ዙሪያ ለሰራተኞች የተሻለ ግንዛቤ ለመፍጠር የሚያስችል የአንድ ቀን ስልጠና ተሰጥቷል፡፡
በስልጠናውም የሰው ሀብት ልማት አስተዳደር ዳይሬክተር አቶ ሀብቴ ነሪ ‹‹ስራ ምንድነው?›› በማለት የመነሻ ሃሳብ ያቀረቡ ሲሆን የስራ ትርጉምን አስመልክተው ሰፋ ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ከዚህም ጋር አያይዘው የሥራ ሰዓት አከባበርና አተገባበርን አስመልክተው ሲገልጹ ማንኛውም የመንግስት ሰራተኛ በቀን 8 ሠዓት የመስራት ግዴታ እንዳለበት በመግለጽ ሰራተኞች በመደበኛው የስራ ሰዓት በአግባቡ መገኘታቸውን ለማረጋገጥና ለመቆጣጠር ያመች ዘንድም ዩኒቨርሲቲው ከዚህ ቀደም ይጠቀምበት የነበረውን አሰራር በማሻሻል እና በቴክኖሎጂ የተደገፈ እንዲሆን በማሰብ የጣት አሻራ አቴንዳንስ በባዮ ሜትሪክስ ማሽን እንዲተገበር ተደርጎ ላለፈው አንድ ዓመት ሲሰራበት መቆየቱን አቶ ሀብቴ ገልጸው በአንጻሩ ግን በርካታ የአፈፃፀም ችግሮች እንደነበሩት አስታውሰዋል ፡፡
አቶ ሃብቴ አክለውም በአፈጻጸም ረገድ የታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ቴክኖሎጂውን አስመልክቶ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተከታታነት ያላቸው ስራዎች በመሰራታቸው ችግሩ እንደሚቀረፍ ያላቸውን ዕምነት ገልጸው ሰራተኞች በቀጣይ በጣት አሻራ አቴንዳስ መገልገያ በሆነው የባዮሜትሪክስ ማሽን በአግባቡ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል ፡፡
በአፈጻጸም ረገድ የሚታዩ ችግሮችን አስመልክቶ በተለይም ከመብራት መቆራረጥ ፣የኮቪድ መተላለፊያ መንገዶች ላይ ትኩረት አድርጎ ከመስራት አንጻር፣ የፈረቃ ሰራተኞችን በተመለከተ የተለያዩ ጥያቄዎች በተሳታፊዎች የተነሱ ሲሆን ምላሽም ተሰጥቶባቸዋል፡፡
በመጨረሻም ከታህሳስ ወር 2014 ዓ.ም ጀምሮ የአስተዳደር ሰራተኞች ደመወዝ ክፍያ በባዮሜትሪክስ ማሽን (በጣትአሻራ) እንደሚሆን ተገልጿል፡