ዩኒቨርሲቲው ከ2018 እስከ 2022 ድረስ ባሉት አምስት ዓመታት ውስጥ ለመተግበር ያዘጋጀውን ስልታዊ ዕቅድ በተመለከተ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል፡፡
የውይይት መድረኩን በንግግር የከፈቱት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር ፋሪስ ደሊል እንደገለጹት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲቋቋሙ በዋነኝነት ትኩረት የሚያደርጉት ብቁና ተወዳዳሪ ምሩቃንን ማፍራት፣ ችግር ፈቺ ምርምሮችን ማካሄድና ከተልዕኮቻቸው ጋር የተገናኙ ስራዎችን መስራት መሆኑን ጠቅሰው ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ለመስራት ከዕቅድ ጀምሮ በዚህ መልኩ በጋራ መወያየት በእጅጉ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ፕሬዝዳንቱ አያይዘውም ዩኒቨርሲቲው ያለፉት አምስት ዓመታት (ከ2013 እስከ 2017) ስልታዊ እቅድ ትግበራውን አጠናቅቆና የነበሩትን አፈጻጸሞችን በጥልቀት ገምግሞ የቀጣይ አምስት ዓመት ( ከ2018 እስከ 2022) ያለውን አዘጋጅቶ ለባለድርሻ አካላት ግንዛቤ ለመፍጠርና መጨመር የሚገባቸውን ግብዓቶችን ለመውሰድ እንዲረዳ ታስቦ ይህ መድረክ መዘጋጀቱን በመግለጽ ከውይይት መድረኩ ጠቃሚ ነጥቦች እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
ከፕሬዝዳንቱ ንግግር በማስከተል የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የ2017 ዓ.ም. በጀት ዓመት ዓመታዊ ዕቅድ አፈጻጸም ፣ ከ2013 እስከ 2017 ድረስ ያለው የግንባታ ፕሮጀክቶች እቅድ አፈጻጸምና የቀጣይ አምስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ ዝግጅት ለባለድርሻ አካላቱ በዝርዝር ቀርቧል፡፡
በቀረበው ዝርዝር የአፈጻጸም ሪፖርትና የእቅድ ዝግጅት ዙሪያ በአምስት ዋና ዋና ነጥቦች ላይ ትኩረት ያደረገ ውይይት ተካሂዷል፡፡ በውይይቱ ላይ ትኩረት የተደረገባቸው ነጥቦች፡-
1.ከመማር ማስተማር ጋር በተያያዘ የትምህርት ጥራት፣ተደራሽነትና ተግባር ተኮር ትምህርት አንጻር የተቋማት ሚና
2.ባሉት የትምህርት ፕሮግራሞች የማስተማር ሞዳሊቲ፣ የመማር ፍላጎት መቀነስ መንስዔና መፍትሄዎቻቸው
3.አሳታፊነትን፣ ተደራሽነትን፣ሀገር በቀል እውቀትን፣ ቴክኖሎጂን ከመቅዳት አንጻር፣ ከተቋም ጋር ትስስር ከመፍጠር ጋር በተያያዘ የምርምር ስራዎችና የቴክኖሎጂ ሽግግር ያለበት ሁኔታ
4.ጥራት፣ ተደራሽት ፣ አሳታፊነት መሰረት ያደረገ የማህበረሰብ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያሉ አስቻይ ሁኔታዎች ፣ ተግዳሮቶችና መፍትሄዎቻቸው
5.ከአገልግሎት አሰጣጥ፣ ከአካባቢው ማህበረሰብ ጋር ትስስር ከመፍጠር ጋር ተያይዞ በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ያሉ ተግዳሮቶችና መፍትሄዎቻቸው በሚሉት ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የባለድርሻ አካላቱ ሰፊ የሆነ ውይይት በማድረግ ጠቃሚ የሆኑ ሃሳቦችን አንስተዋል፡፡
በማጠቃለያው ላይ ዶክተር ፋሪስ ደሊል እንደገለጹት ተሳታፊዎቹ ዩኒቨርሲቲው እስካሁን ለሰራቸው አበረታች ስራዎች ዕውቅና በመስጠታቸው መደሰታቸውን በመግለጽ በቀጣይ በትብብር ተደራሽነትን በማስፋት ስራ ላይ በተለይም ቋንቋን በማበልጸግ፣ የሀገር በቀል ዕውቀትን በጥናት አስደግፎ በመስራት ፣ በስርዓተ ትምህርት ክለሳ ላይ ዩኒቨርሲቲ ሊያተኩርባቸው የሚችልባቸው ዘርፎች ላይ አጽንኦት በመስጠት ፣ በተቋሙ ውስጥ ያለውን ሙያዊ አቅም ለማህበረሰቡ ተደራሽ በማድረግ፣ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ያለውን የሰላም እሴት ይበልጥ ለማጠናከር እንዲረዳ በተለይም በባህላዊ ዳኝነት ላይ በትኩረት በመስራት በአጠቃላይ ተናብቦ ፣ ተባብሮ በመስራት ረገድ እንደተቋም መሰራት ያለባቸውን ጠቃሚ መረጃዎች ከመድረኩ መገኘቱን ገልጸዋል፡፡
የባለድርሻ አካላቱ ከውይይቱ በኋላ ግንባታው በመጠናቀቅ ላይ የሚገኘውን የአስተዳደር ህንፃ እና አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘውን የህጻናት ማቆያ ተዟዙረው ጎብኝተዋል፡፡
በውይይት መድረኩ ላይ ከጉራጌ ዞን ፣ ከምስራቅ ጉራጌ ዞን፣ ከየም ዞን ፣ ከቀቤና ልዩ ወረዳ የተውጣጡ የስራ ሃላፊዎችና ከልዩ ልዩ ተቋማት የተወከሉ የባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
ለጥበብ እንተጋለን !
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ስራ አስፈጻሚ ቢሮ