በጉብሬ ክፍለከተማ ለተደራጁ ( ይስሬሸ የተቀናጀ የግብርና ልማት ህብረት ስራ ማህበር) ስራ አጥ ወጣቶች የሚሆን በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት አማካይነት የተቀናጀ የዓሳ፣ ዶሮ እና የጓሮ አትክልት ልማት ለምግብ ዋስትና በሚል ተሰርቶ የተጠናቀቀ ፕሮጀክት በጉብርየ ክፍለ-ከተማ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አማካኝነት ለተደራጁ ወጣቶች ዩኒቨርሲቲው በዛሬው ዕለት አስረክቧል::
በርክክቡ ወቅት የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንት አባላት፣ የክፍለከተማው የስራ ኃላፊዎች፣ የተደራጁ ወጣቶች እና ፕሮጀክቱን ሲያስተባበሩ የነበሩ መምህራን ተገኝተዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ፋሪስ ደሊል በርክክቡ ስነስርዓት ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ይህ የተጀመረው የወጣቶች የስራ ዕድል ተጠቃሚነት ጅምሩ የሚበረታታ መሆኑን ገልጸው የዚህ እድል ተጠቃሚ የሆኑት ወጣቶች ይበልጥ ሊበረታቱ እንደሚገባና የበለጠ በስራው ላይ በስፋት በመሳተፍ ለሌሎችም አርአያ መሆን እንደሚገባቸው አደራ ብለው ዩኒቨርሲቲውም በቀጣይ በቂ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግላቸው ቃል ገብተዋል።
በወልቂጤ ከተማ ጉብርየ ክፍለከተማ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ኃላፊ የሆኑት አቶ ፈለቀ ገብረስላሴ በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ላበረከተው አስተዋጽኦ አመስግነው የፕሮጀክቱን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያደርጉና ወጣቶቹ ጠንክረው በመስራት በከተማው ምሳሌ የሚሆን ፕሮጀክት እንዲሆን ተገቢውን ክትትል እንደሚያደርጉ ገልጸዋል፡፡
ከዚሁ የልማት ፕሮጀክት ርክክብ ስነስርዓት ጎን ለጎን የዩኒቨርሲቲው የማኔጅመንት አባላት በዋቤ ችግኝ ጣቢያ በመገኘት በጣቢያው የተዘጋጀው ለክረምት አረንጓዴ ልማት የሚውሉ የአገርበቀል ዛፍ ችግኝ ልማት ስራ ያለበት ሁኔታ የጎበኙ ሲሆን በጉብኝቱ ወቅት ዶክተር ፋሪስ ደሊል በሰጡት አስተያየት የችግኞቹ አዘገጃጀት በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸው በቀጣይ በሚሰሩት ስራዎች ላይ ሰፊ ትኩረት በመስጠት ማህበራትና የተለያዩ ድርጅቶች ከወዲሁ የስራ ድርሻ ተሰጥቷቸው አንድም ችግኝ ሳይባክን ለታለመለት ዓላማ መዋል እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል፡፡
በጉብኝቱም ወቅት የፕሮጀክቱ አስተባባሪዎች ከመቶ ሺህ በላይ ችግኞችን ለማፍላት ማቀዳቸውን አሳውቀዋል።
ለጥበብ እንተጋለን!
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት