በጀፚረ ቅርስ አጠባበቅ ዙሪያ በሀገር በቀል ዕውቀት ልማት ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀው የምክክር መድረክ በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ፡፡ “ጀፚረን የመሰሉ እንቁ ቅርሶቻችንን ተንከባክበንና ጠብቀን ለትውልድ እናስተላልፍ” በሚል መሪ ቃል በተካሄደው በዚህ የምክክር መድረክ ላይ የጉራጌ ዞን አስተዳደር ተወካይ፣የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ፣ የጉራጌ ዞን የሴቶች ወጣቶችና ህጻናት መምሪያ ሀላፊ፣ በጉራጌ ዞን ከሚገኙ 16 ወረዳዎች የተውጣጡ የባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤት ሃላፊዎች፣ የጉራጌ የባህል ሸንጎ አባላት እና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት በምክክር መድረኩ ላይ ተሳትፈዋል፡፡
የምክከር መድረኩን በንግግር የከፈቱት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር ፋሪስ ደሊል ሲሆን ዶክተር ፋሪስ በንግግራቸው ላይ እንደገለጹት ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው ጎን ለጎን የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት አካል በሆነው የሀገር በቀል ዕውቀት ላይ ዩኒቨርሲቲው ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸው በጥናትና ምርምር ተለይተው ከሚሰሩ የማህበረሰብ አገልግሎቶች አንዱ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ስራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ዶክተር ፋሪስ አያይዘውም የጉራጌ ማህበረሰብ እንደሌሎች የሀገራችን ህዝቦች ሁሉ የአኩሪ ባህል ባለቤት መሆኑን አስታውሰው ከእነዚህም አኩሪና ከሚዳሰሱ ባህላዊ ቅርሶች መካከል አንዱ ጀፚረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ጀፚረ ከዘመናዊ ምህንድስና የማይተናነስ በመንደሮች መካከል የሚያልፍ ግርማ ሞገስን የተላበሰ ጥበብ መሆኑን ዶክተር ፋሪስ በንግግራቸው ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ዶክተር ፋሪስ እንደገለጹት በጉራጌ ታሪክ ጥንት መሬት የሚከፋፈለው በዘፈቀደ ሳይሆን በባህሉ በተመረጡ አባቶች እና የመሬት ልኬት ዳኞች አማካይነት መሆኑን ገልጸው “ጎጎት” መጽሀፍን ዋቢ በማድረግ እንደገለጹት ጀፚረ ስፋቱ12 ዘንግ መሆኑንና ርዝመቱ ግን በመሀል የሚያልፍ ወንዝ ፣ ገደል ወይም ደን እስከሌለ ድረስ ሳይቋረጥ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡
ዶክተር ፋሪስ በተጨማሪ እንደገለጹት ጀፚረ የለቅሶ ስርዓት የሚፈጸምበት፣እግረኛና ፈረሰኛ ሙሾ የሚደረድርበት፣የሰርግ ስነስርዓት ሲኖር የሙሽሪትና የሙሽራ አጃቢ ወገኖች በዘፈንና በግጥም የሚሞጋገሱበትና በሽማግሌዎች የሚባረኩበት፣ሙሽሮች አጋጌጣቸው የሚታይበትና ውበታቸው ጎልቶ የሚወጣበት፣በእናቶችና አባቶች የሚመረቁበት፣ሕጻናት እንዳሻቸው የሚቦርቁበት ፣ ጎረምሶች የገና ጨዋታ የሚጫወቱበት፣ ዳመራ የሚደመርበት፣ወጣቶች የፈረስ ጉግስ የሚለማመዱበት፣ በቅሎና ፈረስ የሚገራበት፣ኮርማዎች እርስ በርሳቸው የሚፈታተሹበትና የሚያጓሩበት እንዲሁም ሽማግሌዎች ባህላዊ ዳኝነት የሚያካሂዱበት መሆኑን በዝርዝር ገልጸዋል፡፡ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲም ለዚህ ታሪካዊ ቅርስ ትልቅ ቦታ በመስጠት ጀፚረ በሀገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅናን እንዲያገኝ በማሰብ ፡-
1ኛ) በዩኒቨርሲቲው ማስተር ፕላን ላይ ጀፚረ በዲዛይን መካከተቱን
2ኛ) ጀፚረንዳ በሚል ስያሜ በወልቂጤ ኤፍ ኤም 89.2 ሬዲዮ በሳምንት ሁለት ቀን የሚተላለፍ ፕሮግራም መጀመሩን
3ኛ) በቀጣይ ዓለም አቀፍ ስርጭት ሊኖረው የሚችል “ Jofere Ethiopian Journal of Applied Sciences” የሚል የጆርናል ህትመት ለማስጀመር በዩኒቨርሲቲው ሴኔት መጽደቁን
4ኛ) የዩኒቨርሲቲው ሎጎ ሙሉ በሙሉ ጀፚረን የሚገልጽ መሆኑን ዶክተር ፋሪስ በዝርዝር ገልጸው ይህ እንቁ የሆነው ቅርስ ለተለያዩ ሰው ሰራሽ አደጋዎች መጋለጡን በማስታወስ ይህንን መነሻ አድርጎ ዩኒቨርሲቲው የምክክር መድረኩን ማዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ ከዶክተር ፋሪስ ደሊል የመክፈቻ ንግግር በኋላ “Tracing Jefore’s Features, Provisions, intervention and Restoration” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሁፍ በዩኒቨርሲቲው የSociology ትምህርት ክፍል መምህር በሆኑት በመምህር አብነት ሺፈራው የቀረበ ሲሆን በቀረበው ጥናታዊ ጽሁፍ ላይ ሰፋ ያሉ ውይይቶች ተካሂደውበታል፡፡
በምክክር መድረኩ ማጠቃለያ ላይ እንደተገለጸው ጀፚረ እጅግ አሳሳቢ በሆነ ደረጃ ላይ ስለሚገኝ ከፍተኛ የሆነ ጥንቃቄ ሊደረግለት እንደሚገባ፣ የጉራጌ ማህበረሰብ የጀፚረ ባለቤት ስለሆነ ጀፚረን ሊንከባከበው እንደሚገባ፣ የባህል ሸንጎ አባላቶቻችን በትኩረት መስራት እንዳለባቸው፣የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ከወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ጋር በጋራ በመሆን ጀፚረን በባህላዊ ቅርስነት በዩኔስኮ ለማስመዝገብ ጥረት ቢደረግ፣ለጀፚረ ዕውቅና ሊሰጠው እንደሚገባ፣ ጀፚረን በተስተካከለ መንገድ እያቆዩ ያሉት የማህበረሰብ ክፍሎች ዕውቅና ቢሰጣቸው፣ ለጀፚረ የይዞታ ማረጋገጫ ቢዘጋጅለት፣ በጀፚረ ላይ ጥናቶች በስፋት ቢሰሩ፣ የህግ ማዕቀፍ ቢዘጋጅለት፣መንገድ ሲሰራ ዲዛይኑ ላይ የጉራጌ ባህላዊ ሸንጎ አባላት እንዲሳተፉና አስተያየት እንዲሰጡ ቢደረግ፣ መዋቅራዊ ጥበቃ ቢደረግለት፣ መሰረተ ልማቶች ሲገነቡ ቅንጅታዊ አሰራሮች ቢፈጠሩ የሚሉና ሌሎችም አስተያየቶች በምክክር መድረኩ ላይ ተነስተዋል፡፡ በመጨረሻም የምክክር መድረኩ ተሳታፊዎች በቸሀ ወረዳ፣ በፈረዝዬ ቀበሌ አንዛናባጥ በተሰኘ መንደር ተገኝተው የችግኝ ተከላ አከናውነዋል፡፡