ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ምህንድስና እና የሂሳብ ማዕከሉ ለ5 ሳምንታት በቅዳሜ እና እሁድ መረሃ-ግብር ሲሰጥ የነበረውን የመሰረታዊ የኤሌክትሮኒክስ እና የኮምፒውተር ክህሎት ስልጠና አጠናቀቀ
የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ክፍሌ ለንቲሮ እንደገለጹት ስልጠናው ከጉራጌ ዞን ከተማ አስተዳደር እና አቅራቢያ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ከክፍላቸው አብላጫ ውጤት ያላቸው የ9፣10፣11 እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎች ተሳትፈዋል ብለዋል፡፡
ዳይሬክተሩ አክለውም ከዚህ በፊት በተቋሙ ባሉት ቤተ-ሙከራዎች በክረምት መረሃ-ግብር ብቻ ይሰጥ የነበረው የስቴም ፕሮግራም ስልጠና አሁን ላይ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ምህንድስና እና የሂሳብ ማእከል ሁለት ተጨማሪ ላቦራቶሪዎች በመኖራቸው ብዙ ቁጥር ያላቸውን ተማሪዎች በማሳተፍ ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ እንዲያስችል በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት (በቅዳሜ እና እሁድ) መረሃ-ግብር በመጀመሪያ ዙር 35 ተማሪዎችን ማሰልጠን ተችሏል ብለዋል፡፡
ፕሮግራሙን ያስጀመሩት የዩኒቨርሲቲው የምርምር እና ማህበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዝዳንት ዶክተር ዮሃንስ ገብሩ ስልጠናው ተማሪዎች ያሏቸውን እምቅ እውቀት እና ተሰጥኦ ይበልጥ እንዲያዳብሩ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል፡፡ ዶ/ር ዮሃንስ አክለውም ተማሪዎች ካሰቡበት እንዲደርሱና ስኬታማ ህይወት እንዲኖራቸው የፈጠራ ስራዎቻቸውን በሚሰሩበት ጊዜ በፕሮግራም እና በዲሲፕሊን እንዲመሩ አሳስበዋል፡፡
በፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ሃብቴ ዱላ ባስተላለፉት መልዕክት ሰልጣኝ ተማሪዎች ታዳጊ እና ባለ ብህ አእምሮ በመሆናቸው ያሏቸው ተሰጥኦዎች ለማዳበር በየቀኑ ልምምድ በማድረግ አዳዲስ ስራዎችን ሊፈጥሩ እንደሚገባ ጠቅሰው በዩኒቨርሲቲው በነበራቸው ቆይታም ከመምህራን ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመለወጥ ሃገር የምትጠብቅባቸውን ሃላፊነት እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡
ዶ/ር ሃብቴ አክለውም ተማሪዎቹ የፈጠራ ስራ ለመስራት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማስቻል እንደ ተቋምም እንደ ግልም ድጋፋቸው እንደማይለያቸው ቃል ገብተዋል፡፡
በእለቱም ተማሪዎቹ በነበራቸው ቆይታ የሰሯቸውን ፕሮጀክቶች ያቀረቡ ሲሆን ከታዳሚው ሃሳብ አስተያየት እንዲሁም ጥያቄዎች ተነስተው ምላሽም ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ተማሪዎችም በዩኒቨርሲቲው በነበራቸው ቆይታ ጥሩ እውቀት ገብይተናል ሲሉ በስልጠናውም የነበረንን ችሎታ ለማዳበር አግዞናል በማለት በቀጣይም አዳዲስ የፈጠራ ስራዎችን በመስራት አራዕያ ለመሆን እንጥራለን ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡