ከወልቂጤ ከተማ እና ከአካባቢው የተወጣጡ ድጋፍ የሚሹ አረጋውያን እና ህፃናት በዩኒቨርሲቲው ዋናው ግቢ ከዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ጋር የፋሲካን በዓል በጋራ በመሆን በድምቀት ማክበራቸውን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ህብረት የህዝብ ግንኙነት ዘርፍ በማህበራዊ ትስስር ገጹ ላይ ገልጿል፡፡ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ እና የዩኒቨርሲው የተማሪዎች ህብረት የበጎ-አድራጎት ዘርፍ በጋራ በመተባበር ያዘጋጁት ይህ ታላቅ የፋሲካ በዓል ፕሮግራም "ዛሬን ያየነው በእናንተ ትከሻ ላይ ቆመን ነው!" በሚል መሪ ቃል የተከበረ ሲሆን ቁጥራቸው ከ300 በላይ የሆኑ ድጋፍ ለሚሹ አረጋውያን እና ህፃናት ማዕድ በማጋራት፣ ከ35 ኩንታል በላይ የጤፍና የስንዴ እንዲሁም የተለያዩ ቁሳቁሶችን ድጋፍ በማድረግ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በዓሉ በድምቀት ተከበሯል፡፡
በፕሮግራሙ ላይ በመገኘት የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው የም/ማ/አገ/ም/ፕሬዝዳንት የሆኑት ዶ/ር ዮሃንስ ገብሩ ባስተላለፉት መልዕክት ለአረጋውያኑና ለህፃናቱ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክታቸውን ካስተላለፉ በኋላ ከዩኒቨርሲቲው ጋር በመቀናጀት ይህንን ፕሮግራም ላዘጋጁት የተማሪዎች ህብረት አመራሮች ምስጋናቸውን በማቅረብ ዩኒቨርሲቲው በቀጣይ ተመሳሳይ የሆኑ ድጋፎችን ለአረጋውያኑ እና ለህፃናቱ እንደሚያደርግ ቃል ገብተዋል ።
የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ፅ/ቤት ሀላፊ እና የፕሬዝዳንቱ ተወካይ የሆኑት ረ/ፕ መለሰ እጥፉ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት በቀጣይ ዩኒቨርሲቲው እንደዚህ ዓይነት ወገናዊ ድጋፎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አብራርተው ለተማሪዎች ህብረት ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ህብረት እና የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ሚካኤል ያቦነሽ በበኩሉ ባስተላለፈው መልዕክት ይህ ፕሮግራም የተሳካ እንዲሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱት የተማሪዎች ህብረት አመራሮች ፤ ልዩ ልዩ አልባሳት ድጋፍ ላደረጉ ተማሪዎች፣ መምህራንና ሰራተኞች፣ እንዲሁም ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ላደረገው ድጋፍ ምስጋናውን አቅርቧል።