የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ከጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ እና ትምህርት ቤቶች ከተውጣጡ ባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል።
በመድረኩ የውይይት መነሻ ሀሳብ እንዲሆን "የበጎ ስብዕና መሸርሸር ተግዳሮቶች፤ በታዳጊዎች ባህሪ እና ትምህርታዊ እድገትን ዙሪያ የአዎንታዊ የባህሪ ድጋፍ አስፈላጊነትን" የዳሰሱ ጽሁፎች በዩኒቨርሲቲው መምህራን መ/ር በቃሉ ዋቸሶ እና መ/ር ናሆም ሰለሞን ቀርቧል።
በተሳታፊዎችም በርካታ ገንቢ ሀሳብ ፣ አስተያየቶች እና ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን ምላሽም ተሰጥቶባቸዋል።
የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ ሳይንስና ስነ-ሰብ ኮሌጅ ዲን አቶ ታኖ ገትር ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽ በሰጡበት ወቅት የተማሪዎች ውጤትና የወጣቶች ስነ-ምግባር ማሽቆልቆል ጉዳቱ የተማሪዎችና የወጣቱ ብቻ ሳይሆን የማህበረሰቡም ጭምር ነው በማለት ችግሩን ለመቅረፍ የሚመለከታቸው አካላት በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አስከብር ወልዴ በበኩላቸው በትምህርት ዘርፉ የሚስተዋለውን የተማሪዎች የትምህርት ውጤትና የወጣቶችን ስነ- ምግባር ለማሻሻል የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ርብርብ የሚጠይቅ በመሆኑ በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ክፍሌ ለንቲሮ ፕሮግራሙን ሲያጠቃልሉ እንደተናገሩት አሁን ላይ ያለው የታዳጊው ስነ-ምግባር ለሀገር ስጋት እንዳይሆን ሁሉም ዜጋ ሀላፊነቱን በአግባቡ በመወጣት የድርሻውን እንዲያበረክት የጠየቁ ሲሆን የውይይቱ ተሳታፊዎችም ከመድረኩ ያገኙትን ግብዓት ተግባር ላይ በማዋል የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማበርከት ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።