የዩኒቨርሲቲው የሴቶች ህጻናት እና ወጣቶች ኤች.አይ.ቪ ኤድስ መከላከል እና መቆጣጠር ዳይሬክቶሬት ከተማሪዎች ህብረት ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ112ኛ ጊዜ በሀገራችን ለ47ኛ ጊዜ እየተከበረ የሚገኘው ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን (ማርች-8) “ፈጠራና ቴክኖሎጂ ለጾታ እኩልነት” በሚል መሪ ቃል በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ተከብሯል፡፡
ፕሮግራሙን በንግግር የከፈቱት የዩኒቨርሲቲው የሴቶች ህጻናት እና ወጣቶች ኤች.አይ.ቪ ኤድስ መከላከል እና መቆጣጠር ዳይሬክተር የሆኑት ወ/ሮ መሰረት አስራት ቀኑን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሴቶች መብት መከበር ከመጀመሩ በፊት በጉራጌ ማህበረሰብ ዘንድ የሴቶች መብት ተሟጋች የነበረችው የቃቄ ውርድዎት ለሴቶች መብት መከበር ታደርግ የነበረውን ትግል እና የነበራትን ሚና አስመልክተው ለታዳሚዎች ገለጻ አድርገዋል፡፡
ዳይሬክተሯ አያይዘውም ሴት ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው በሚኖራቸው ቆይታ የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች እንዴት መፍታት እንደሚችሉ የሚያግዙ የተለያዩ ስልጠናዎች እየተሰጣቸው እንደሚገኝ አስታውሰው ከመደበኛ የትምህርት ሰዓታቸው ውጪ የሚኖራቸውን ጊዜ ወደ ዜሮ ፕላን ማዕከል በመሄድ እንዲያሳልፉና የተለያዩ ተሞክሮዎችንና ልምዶችን የሚለዋወጡበትን መድረክ በአግባቡ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡
በፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የጤና ሳይንስ ኮሌጅ መምህርት የሆኑት መምህርት እስከዳር ተመራቂ ተማሪዎች በሚኖራቸው የመውጫ ፈተና( EXIT EXAM) ዙሪያ ለታዳሚዎቹ ሰፋ ያለ የግንዛቤ ማስጨበጫ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
በዕለቱም ከ8 ኮሌጆች እና ከ1 ትምህርት ቤት ከየትምህርት ክፍላቸው አብላጫ ውጤት ላመጡ ሴት ተማሪዎች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
በፕሮግራሙ ላይ የተቋሙ መምህራን እና የአስተዳደር ሰራተኞች እንዲሁም ሴት ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን በፕሮግራሙ ማጠቃለያ ላይ በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ በመገንባት ላይ ያለው የህጻናት ማቆያ በፕሮግራሙ ተሳታፊዎች ተጎብኝቷል፡፡
ለጥበብ እንተጋለን!
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት