በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከህዳር 8 - 10/2015 ዓም ሲካሄድ በቆየው 31ኛው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባኤ መጠናቀቅን ተከትሎ የኢፌዲሪ ትምህርት ሚኒስቴር የ2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት መልቀቂያ ፈተና አሰጣጥ ሂደት ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ዩኒቨርሲቲዎች፣ የፀጥታ አካላት፣ የትምህርት ቢሮዎች እና ሌሎች በሂደቱ አበርክቶ ለነበራቸው ተቋማት ምስጋና እና እውቅና በሰጠበት መድረክ ላይ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ደረጃ ማጠናቀቂያ (የ12ኛ ክፍል) ስኬታማ ሆኖ እንዲጠናቀቅ በማድረግ ረገድ ላበረከተው ሁሉን አቀፍ አስተዋጽኦ ከትምህርት ሚኒስቴር የምስጋና የምስክር ወረቀት ተበርክቶለታል፡፡
በ31ኛው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባኤ ላይ ዶክተር ፋሪስ ደሊል የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት፣ ዶክተር ሀብቴ ዱላ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንትና ተማሪ ሚካኤል ያቦነሽ የኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት እና እንዲሁም የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ዩኒቨርሲቲያችንን ወክለው በጉባዔው ላይ ተሳትፈዋል፡፡
ባለፉት ሶስት ቀናት በተካሄደው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባዔ ላይ ባለፉት ዓመታት በትምህርት ዘርፉ የተከናወኑ ተግባራት ከትምህርት ጥራት፣ አግባብነት፣ ፍትሀዊነት፣ ተሳትፎና ተደራሽነት ጋር የተያያዙ በርካታ ተግባራት የተመዘገቡ መሆኑን በመጥቀስ በትምህርት አማካሪ ካውንስሉ የተዘጋጁ የኢትዮጵያን የትምህርት ገጽታና አመላካች አቅጣጫዎች የሚያሳዩ ጥናታዊ ጽኁፎች ላይ የትምህርት ዘርፉ የመጣበትን ጉዞና ቀጣይ አቅጣጫዎች የታየበት መሆኑን ጉባዔው አጽንኦት በመስጠት፣ የመምህራን ማህበርና የትምህርት ልማት አጋር ድርጅቶች ሪፖርቶች የትምህርት ዘርፉን ለመደገፍ ያከናወኑት ተግባራት የቀረቡበት መሆኑን በማስታወስ ፣ የትምህርት ዘርፉ የሪፎርም ስራዎችና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ የተያዘ መሆኑን ጭምር ከግምት በማስገባት ጉባዔው ባለስምንት ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቋል፡፡
ይህ የ31ኛው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባዔ በሲዳማ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሃዋሳ ከተማ የተካሄደ ሲሆን
Ø ከህዝብ ተወካዮች ምክርቤት
Ø የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት ተወካዮች
Ø የልዩ ልዩ የፌደራል መስሪያ ቤቶች ተወካዮች
Ø የክልል/የከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮዎች አመራሮች
Ø የዩኒቨርሲቲ አመራሮች
Ø የተለያዩ ማህበራትና አደረጃጀቶች ተወካዮች
Ø የትምህርት ልማት አጋር ድርጅቶች ተወካዮች በጉባዔው ላይ ተሳትፈዋል፡፡
ለትምህርት ጥራት የጋራ ጥረት!
ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህ/ው/ግንኙነት ዳይሬክቶሬት