የኢፌዴሪ የትምህርት ሚኒስቴር ሚንስትር የሆኑት ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ ከትምህርት ሚኒስቴር ዴኤታ ከሆኑት ከክቡር ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ ጋር በጋራ በመሆን በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ተገኝተው ከዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ጋር በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የጋራ ውይይት አካሂደዋል፡፡ ከውይይቱ አስቀድሞ ክቡር ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ የአረንጓዴ አሻራቸውን ያኖሩ ሲሆን ከዚህም ክንውን በኋላ ዶክተር ፋሪስ ደሊል የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት የተቋሙን አጠቃላይ ሁኔታ የሚገልጽ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡
በውይይቱም ወቅት እንደተገለጸው የልኡካን ቡድኑ ከዚህ ቀደም 23 ዩኒቨርሲቲዎችን በተመሳሳይ ሁኔታ መጎብኘታቸውን ገልጸዋል ፡፡ ውይይቱ በመሰረታዊነት ያተኮረው በሀገራችን ላይ የሚታየውን የትምህርት ጥራት ችግር መሰረት ባደረገ መልኩ ሲሆን በኢትዮጵያ ያለው የትምህርት ጥራት ችግር አሳሳቢ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ እና በተካሄደው ውይይት ላይ የተገኙት ተሣታፊዎችም ገልጸዋል።ችግሩ ከመጀመሪያ ደረጃ እስከ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተንሰራፋ እንድሆነ ጥናቶችን በመጥቀስ ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ በዝርዝር ገልጸዋል። ፕሮፌሰር ብርሀኑ አያይዘውም ሲገልጹ የኢትዮጵያን የትምህርት ጥራት ለማስጠበቅ
በሚደረገው ጥረት ከ2015 ጀምሮ ተግባራዊ የሚሆነው የከፍተኛ ትምህርት የመውጫ ፈተና አንዱ የመፍትሄ አካል ሆኖ የሚቀጥል እንደሚሆን በውይይቱ ላይ በአፅንኦት አንስተዋል፡፡
ሚኒስትሩ እንደተናገሩት ባለፉት ዓመታት ውስጥ የትምህርት ሥርዓቱ በተጨባጭ ያለበት ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ከመሆኑ አንጻር የተለያዩ ጥናቶችንና ውይይቶችን በማካሄድ አራት ዋና ዋና ችግሮችን መለየት ተችሏል ብለዋል፡፡ ለትምህርት ሥርዓቱ መውደቅ መሠረታዊ ከሆኑ ችግሮች መካከል፡- የትምህርት ጥራት ችግር፣ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት፣ የትምህርትና የክልልተኝነት መያያዝ እና የሞራል ኪሣራ መሆናቸውን ጠቁመው በቀጣይ 5 ዓመታት ውስጥ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡
ሚኒስትሩ አክለውም በቀጣይ አዲስ ዩኒቨርሲቲዎችን የመክፈትና የማስፋፊያ ግንባታዎች የማካሄድ ዕቅድ የሌለ ሲሆን በሂደት ላይ ያሉ ግንባታዎችን የማስጨረስ፣ ያለውን ግብዓት የማሻሻልና ጥራት የማስጠበቅ ሥራ ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ከታችኛው የክፍል ደረጃ ጀምሮ መሥራት ይገባል ያሉት ሚኒስትሩ ባሳለፍነው የትምህርት ዘመን የፈተና ደኅንነትን ለማስጠበቅ ፈተናውን በታብሌት ለመስጠት ሙከራ የተደረገ መሆኑን አስታውሰው በወቅቱ ከገጠመው የበጀት እጥረት የተነሳ ሳይተገበር መቅረቱን ገልጸው በቀጣይ ኩረጃን በማስቀረት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፈተናቸውን በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ተመድበው እንዲፈተኑ ከወዲሁ መታቀዱን ገልጸዋል፡፡ በመጨረሻም ዩኒቨርሲቲዎች ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ነጻ ሆነው የእውነትና የእውቀት ምንጭ እንዲሆኑ ለማስቻል ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ አወቃቀር ጀምሮ ያለው ሥርዓት ሁሉን ባማከለ መልኩ መደራጀቱን እና በቅርብም ተግባራዊ እንደሚደረግ የጠቆሙት ሚኒስትሩ ሁሉም ባለድርሻዎች በጋራ ለለውጥና የተሻለ ትውልድ ለማፍራት እንዲተጉ ከአደራ ጭምር አሳስበዋል፡፡
ከተሰብሳቢዎች የተለያዩ ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን ለተነሱት ጥያቄዎች ክቡር አቶ መሀመድ ጀማል የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ ዶክተር ፋሪስ ደሊል፣ክቡር ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌና ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በተለይም ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ የሰጡት ማብራሪያ እጅግ ማራኪ፣ተዝናኖት የተሞላበት፣መሳጭና ትምህርት አዘል ሆኖ መልዕክቶችን እያዋዙ ያቀረቡበት ዘዴ በእጅጉ የተዋጣለት ነበር፡፡ በመጨረሻም የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳደር እያስገነባ ያለውን አዳሪ ትምህርት ቤት ተዟዙረው ጎብኝተዋ።