በኢፌዴሪ የጤና ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታ እና የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ በሆኑት ክቡር ዶክተር ደረጀ ዱጉማ የተመራው የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ በቡታጅራ ከተማ በመገኘት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የቡታጅራ ካምፓስ ለትምህርት ማስጀመሪያ እንዲረዳ ግንባታው ያለበትን ደረጃ ጎብኝቷል፡፡ በሁለት ሳይት ከሚገኙት ከቀድሞ ቤቶች አስተዳደር የተገዙት ያልተጠናቀቁ ህንጻዎች በማጠናቀቅ በመደበኛ ትምህርት ለማስጀመር የተጀመረው ግንባታ በቅርቡ ማለትም በ2014 ዓ.ም አጋማሽ ለማስተማሪያነት፣ የተማሪዎች ማደሪያነትና ለሌሎች አገልግሎቶች መስጫ እንዲሁም ለቢሮነት እየተገነባ ያለው ግንባታ በተሻለ ሂደት ላይ የሚገኝ ቢሆንም ከሶስት አመት በፊት የተጀመረው ለመምህራን መኖሪያነት እየተገነባ ያለው ግንባታ ግን ሥራው ተቋርጦ በመቆየቱ ዘግይቷል፡፡ ይህ ግንባታ በተቀመጠለት የጊዜ ገደብ ያልተጠናቀቀበት ምክንያት በዋናነት ከይዞታ ይገባኛል ጥያቄ ጋር በተያያዘ ሲሆን ይህንኑ ጉዳይ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት እና የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንት አባላት ከከተማው ከንቲባ እንዲሁም ከሌሎች አመራሮች ጋር በጋራ በመወያየት በአስቸኳይ ችግሩ ተፈትቶ ወደስራ የሚገባበትና ቀሪ ስራዎች ተጠናቅቀው ተቋሙ ተማሪዎችን ለመቀበል በሚያስችል መልኩ ዝግጅቱ እንዲጠናቀቅ በስራ አመራር ቦርዱ አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ በተጨማሪም በቀጣይ አሁን ላይ ያሉት ቀሪ የግንባታ ስራዎች ተጠናቀው ከሚጀመሩት ጥቂት ፕሮግራሞች በተጨማሪ ተገቢነት ያላቸው ፕሮግራሞች ለማስፋፋት የሚያችል ከይዞታ ይገባኛል ጥያቄ ነጻ የሆነ መሬት የከተማ አስተዳደሩ አዘጋጅቶ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ለዩኒቨርሲቲው እንዲያስረክብ በሥራ አመራር ቦርዱ አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ የከተማው ከንቲባም በቂ መሬት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ነፃ የመስሪያ ቦታ ለዩኒቨርሲቲው እንደሚያስረክብ ለሥራ አመራር ቦርዱና ለዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራር ቃል ገብቷል፡፡