ድጋፉ የተደረገው የመኖሪያ ቤታቸው በእሳት ቃጠሎ አደጋ ምክንያት ለወደመባቸው 26 መምህራንና 2 የቸሀ ወረዳ አርሶ አደሮች ሲሆን የተደረገው ድጋፍ 1.7 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው በድምሩ 2560 ቆርቆሮዎች መሆናቸውን የዩኒቨርሲቲው የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ክፍሌ ሌንቲሮ ገልጸዋል፡፡
በድጋፍ ፕሮግራሙ ላይ ከዞኑና ከከተማ አሰተዳደሩ የተውጣጡ የተለያዩ የስራ ሃላፊዎች፣ የመምህራን ማህበር አመራሮችና የመኖሪያ ቤታቸው የወደመባቸው መምህራንና አርሶ አደሮች ተገኝተዋል፡፡ በተለይም ከዞንና ከከተማ አስተዳደሩ የተገኙት አመራሮች በሰጡት አስተያየት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ በተለያዩ ዘርፎች ልዩ ልዩ የማህበረሰብ አገልግሎቶችን እየሰጠ መሆኑን ገልጸው ለአብነትም ልዩ ልዩ የአቅም ማጎልበቻ ስልጠናዎችን በመስጠት፣ በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራሞች የትምህርት ዕድሎችን በማመቻቸት፣ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል ጥረት በማድረግ፣ የተማሪዎችን ስነምግባር ለማሻሻል የሚያግዙ ስልጠናዎችን በመስጠት ረገድ ተቋሙ ሰፊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን በማስታወስ ከዚህ በተጨማሪ ለወገን ችግር ደራሽነቱን በግልጽ በሚያረጋግጥ መልኩ የቤት ንብረታቸው ለወደመባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ዩኒቨርሲቲው ዛሬ ላይ ላደረገው ድጋፍ አመራሮቹ በዞኑና በከተማ አስተዳደሩ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር ፋሪስ ደሊል በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት አደጋው እንደደረሰ የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንት ድጋፉን ለማድረግ መወሰኑን አስታውሰው በተለያዩ ምክንያቶች ድጋፉ ሊዘገይ እንደቻለ ገልጸዋል ፡፡ በተጨማሪም ዶክተር ፋሪስ ደሊል በሰጡት አስተያየት በቀጣይ ተመሳሳይ የሆኑ ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው በተለይም በብር 50.000.000 ( ሀምሳ ሚሊዮን ብር) እየተሰሩ ያሉት የማህበረሰቡን ችግር በዘላቂነት መፍታት የሚችሉት የዉሃ ፕሮጀክቶችን በማጠናከር ስራ ላይ በትኩረት እንደሚሰራ፣ በዞኑ ባሉት ትምህርት ቤቶች ላይ በተለይም በትምህርት ጥራት ላይ ለውጥ ለማምጣት አጫጭር ስልጠናዎችን በመስጠት፣ የመምህራንን አቅም በማጎልበት ላይ ሰፊ ትኩረት በማድረግ፣ በተማሪዎች ዘንድ ከስነምግባር ጋር ተያይዞ የሚታዩ ችግሮችን በጥናት ለይቶ ዘላቂ የሆነ መፍትሄ በማምጣት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡
ዶክተር ዮሀንስ ገብሩ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት ዩኒቨርሲቲው በዞኑ ውስጥ የሚገኙ ልዩ ልዩ መስሪያ ቤቶችን አሰራራቸውን ለማዘመን የሚረዱ ሶፍትዌሮችን በማበልጸግና ድረገጾቻቸውን በማሻሻል ስራ ላይ በስፋት እየተሳተፈ መሆኑን ገልጸው በቅርቡም የጋሶሬ ትምህርት ቤትን በዘመናዊ መልኩ ለመገንባት የሚያግዝ ዲዛይን ያሰራ መሆኑን አስታውሰው በቅርቡም የተሰራው ዲዛይንን በማስተቸት ለሚመለከታቸው አካላት ለማስረከብ በዝግጅት ላይ መሆኑን በመግለጽ በቀጣይ በማህበረሰብ አገልግሎት ስራው ላይ ሰፊ ተሳትፎ ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡